Tuesday, March 29, 2022

ሀገሬን ጎድላ......

 

ሀገሬን ጎድላ አየሁዋት

ሊነጋ ሲል በከባዱና በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ማለፍ፡ ግድ እንደሚሆን ብናምንም፡ ከባዱና ድቅድቅ ጨለማው ግን ለሀገሬ በጣም ረዘመባት፡፡ በትንሽዋ እድሜ ሀገሬ ጦርነት፤ረሀብ ችግርና እንግልት አስተናግዳለች፡፡ ከእኔ ከቀደም ያሉት የሀገሬ ዘመናትም፡ ከአሁኑ ትንሽ ይሻሉ ካልሆነ በስተቀር ችግሮች ነበሩ፡፡ በርግጥ ችግሮች መልካቸውን ይቀይራሉ እንጅ መቼም ቢሆን ከችግሮች ነጻ መሆን አይቻልም፡፡ ግን አንዳንድ ጊዜ ሀገሬ የገጠማት ችግር፡ ከታሪኳና ከእድሜዋ ልክ ሳይሆን ሲቀር አንገት ያስደፋል፤ያሳዝናልም፡፡ እንደክርስቲያን ተስፋ አልቆርጥም የማያንቀላፈው፤ ከአይን ጥቅሻ ፈጥኖ የሚደርሰው አምላክ ፊቱን ወደ እርሷ ባዞረ ጊዜ ግን ችግሮቿ ሁሉ ከእግሯ በታች እንደሚሆኑ አምናለሁ፡፡ ያኔ ታዲያ ችግሮች ሁሉ የተወገዱላት፤ማህበራዊ ፍትህ የሰፈነባት፤ የሁሉም ቤት ትሆናለች ሀገሬ፡፡ ለዚህ እውን መሆን የእኔን ድርሻ ሳልዘነጋው ማለት ነው፡፡

ባለፉት ቀናት በምድረ አረብ ባልተገባ የአኗኗር ዘዴ የሚኖሩት ወገኖቻችን ለማስወጣት መንግስት በከፍተኛ ደረጃ እየሰራበትና፡ ምናልባት ከዛሬ ጀምሮ ወደ ሀገር መመለስ እንደሚጀምሩና ሀገራቸው ሲገቡም ማረፊያ ቦታዎች እንደተዘጋጁ በምስልና በድምጽ ሰምቻለሁ፡፡ መንግስት፤የወሰደው ትክክለኛ መንገድ ይመስለኛል፡፡ ሀገር እናት ናት፡፡ እናት ልጆችዋን ጠዋት ልጄ በሰላም ወጥተህ/ሽ ተመለሽ ብላ ግንባር ስማ፡ በፍቅርና በስስት አይን ትሸሻለች፡ ሲመለሱ እጆችዋን ዘርግታ፡ በእቅፋዋ፡ በዋጋ የማይተመነውን ፈገግታ ለግሳ፡ በጸሐይ የጠቆረውን ፊት አብሳ እንኳን ደህና መጣችሁ ብላ የውጭውን መከራና ድካም በአንዴ እንደምታስረሳው፡ ሀገርም ይህንን ለዜጎችዋ ብታደርግ እሰይ ያሰኛል እንጂ ለምን አያስብልም፡፡ እናት ለሚረብሸውም፤ለጨዋውም፡ ለሰነፉም ለጎበዙም ልጅ ያላት ፍቅርን እንክብካቤ አንድ ነው፡፡ ሰነፍ ስለሆንክ ቁርስ አትበላም አትልም፡ ተገቢውን ቁጣና ምክር ትሰጣለች እንጂ፡፡ ሀገርም ይህንን ማድረግ ሲጠበቅባት በዚህ በኩል ጎድላ አይቻታለሁ፡፡

ከበርካታ ቦታዎች ህገወጥ ተብለው በተፈረጁ ቡድኖችና በህጋዊ መዋቅር ስር ሆነው ህገወጥን ስራ በሚደግፉና በሚያበረታቱ ባለጊዜዎች የተነሳ በርካታ ሚስኪን ወገኖቻችን መከራ ደርሶባቸዋል፡፡ ከሞትም የከፍ ሞትና እንግልት ደርሶባቸዋል፡፡ ያለ እድሜያቸውና በማያውቁት ጉዳይ የተገደሉ፤ አካላቸው የጎደለ፤ ባልጸና እግራቸው፡ የማይደፈረውን የስደት ኑሮ የተጋፈጡ በርካታ ህጻናቶችን፡ አይተናል፡፡ እነዚህ ህጻናት አድገው ጤነኛ ዜጋ ስለመሆናቸው ማንም እርግጠኛ መሆን አይችልም፡፡ በንጹህ ህሊናቸው ያዩት ግፍና መከራ በህሊናቸው ታትሞ ነገ ለበቀል፡እንደማይነሱ ማንም ማስረጃ መስጠት አይችልም፡፡ ይባስ ብሎ መከራን ሸሽተው ሰላም ነው ወደሚሉት አካባቢ ቢደርሱም ሰላም ያሉት፤ያስጠጋኛል ያሉት ሀገርና ወገን ግን ወደዚህ ወደዚያ እያደረገ መከራውን ሲያበዛባቸው፡ ያሉ ዜጎቻችን፡ችግራቸው፡ በእጅጉ እንደሚገዝፍ ማንም አያውቀውም፡ብዬ ለመናገር፡ሀገሬንና የሀገሬን ሰው አላውቀው ማለት ነው፡፡ ይህች ሀገር እኮ እንግዳ ሲመጣ አልጋውን ለቆ፡ እግር አጥቦ፤ ለእርሱ ፡ዘወትር፡የማይጠቀምበትን ቁሳቁስና ምግብ ለእንግዳው የሚሰጥ ህዝብ ያለባት ናት፡፡ ዛሬ በዚች ሀገር በሁሉም ቦታዎች በስደተኛ ጣቢያዎቹ እየተንገላቱ ያሉ በርካታ ህዝቦች አሉ፡፡ እነርሱን በድንኳን ተቀብላ ለማስተናገድ ቀና ያልሆነች ሀገር ከስደት ተመላሾችን ፍራሽ ዘርግታ ለመቀበል ቀናደፋ ስትል፡ ሀገሬ ሆይ እንድል አስገድዶኛል፡፡ በሀገር የተፈናቀለው፡ አምራች፤የሀገር ዋልታና ማገር የሆነው ገበሬውና ቤተሰቦቹ ናቸው፡፡ ገበሬውና ቤተሰቦቹ ከአረብ ሀገር ካሉ ስደት ተመላሽ ዜጎች አያንሱም አይበልጡምም፡፡ እርሱም ንጹህ ፍራሽ ባይሆንም ከጸሐይ ይጠለልበት ከዝናብ ይከለልበት ድንኳን ይሻል፤ የሚቀምሰውም ምግብ ይሻል፡ ከሁሉም በላይ ተረጋግቶ የሚያርፍበት ቦታ፡፡

መቼም የሀብት እጥረት የሚለው ጉዳይ ለገበሬው ሲሆን ገኖ ይሰማል፡፡ ሀገሬ ሀብት አላጣችም፡፡ ግን ፍትሀዊና ቅደም ተከተላዊ የሀብት ድልድል አለማድረግይመስለኛል ችግሩ፡፡ መከራ በበዛባት ሀገር ውስጥ በየጊዜው በሰፋፋ አዳራሾችና በመናፈሻዎች የሚደረጉ መመሰጋገኛ ፕሮግራሞች፡ የፕሮግራማቸውን ይዘት ሳይለቅ በቅናሽ፤ ሲሆን በሻይ ቡና ብቻ አድርጎ ቀሪውን ወደ ተፈናቃዩ፡ ማድረግ፡ ሀገር ሰላም ስትሆን ሊደረስባቸው የሚችሉ ስራዎችን ማዘግየትና ዜጋን መታደግ ግድ የሚል ይመስለኛል፡፡ ከምን አይነት ልማት የሰው ህይወት ይቀድማል፡፡

ለማንኛውም፡ በስደት አለም የነበራችሁ ወገኖቼ እንኳን በሰላም ተመለሳችሁ ለማለት ነው፡፡



Saturday, March 26, 2022

የ2014 የ12 ከፍል ብሔራዊ ፈተና

                          የ2014 የ12 ከፍል ብሔራዊ ፈተና ገመና

በሀገር ውስጥ በነበረው ግጭትና በኮሮና ምክንያት መደበኛ የፈተና ጊዜውን ሳያከብር በሁለት ዙር የተሰጠው የ 12 ክፍል ብሔራዊ ፈተና ውጤት ከተገለጸበት ከጥቂት ቀናት በሁዋላ ወደ ሀገር አቀፍ ፈተናዎች ኤጄንሲ፡ እና ወደ አንጋፋው የትምህርት ሚኒስቴር  ህንጻ በየቀኑ ሊባል በሚቻል ደረጃ ተመላልሻለሁ፡፡ ሐገር አቀፍ ፈተናዎች ኤጂንሲ ህንጻው በእድሳት ላይ ያለ በመሆኑንና ከፈተና ጋር በተያያዘ ወደ ውስጥ መግባት እጅግ በጣም ከባድ ነበር፡፡ ለተወሰኑ ቀናት ለታክሲ፤ለዳቦ፤ለዘይት እንደሚደረገው ሰልፍ ተሰልፎ መግባትም ተጀምሮ ነበር፡፡ ምንም እንኳ ከውስጥ ያሉት ሃላፊዎችና ባለሙያዎች በአቅማቸው ባለጉዳይን እና ቅሬታን ለመቀበል ጥረት ቢያደርጉም ስህተት ለማረም ግን ያላቸው ተነሳሽነት እጅግ አነስተኛ ነው፡፡ ምን ያክል ጥንቃቄ ተደርጎ እንደተሰራ ያስረዳሉ እንጅ በጥንቃቄ ውስጥ እንኳ፡ሊፈጸም የሚችል ስህተት ስትነግሩዋቸው መስሚያቸው ጥጥ፤ ፊታቸው የነሐሴን ደመና ይመስላል፡፡ ባለጉዳይን ከመሰልቸታቸው የተነሳ፡ ወደ ትምህርት ሚኒስቴር መሔድ የሌለበትን ጉዳይ ከራሳቸው ላይ አዙረው ተገልጋይን በተለይም ክልል አቋርጠው የመጡ ወላጆችን ይልቁንም አካል ጉዳት ያለባቸውን ተማሪዎች ፡ ሲያጉላሉ ለተመለከተ ህዝብን ማገልገል ምንያክል ውሃ እንደበላው ማሳያ መንገድ ነው፡፡ ባለግርማ ሞገሱ ትምህርት ሚኒስቴር ህንጻ ውስጥ ያሉት ባለስልጣናትና በስራቸው ያሉ ከፍተኛ ባለሙያዎች በራሳቸው ተነሳሽነት ባለጉዳይን ሊያስተናግዱ ቀርቶ በስራ ሰዓት ቢሮዋቸው ውስጥ አለመገኘታቸው፡ በስንት ሰኣት እንደሚገቡ እንኳ መረጃ አለመተዋቸው ህሊናን የሚጎዳ ከመሆኑ ባለፈ ችግርን ለመፍታት ያላቸው ተነሳሽነት ተገልጋይ በማማረር ወደ ዚህ ግቢ እንዳይገባ አድርጉ ተብለው ገለጻ የተሰጣቸው ይመስላል፡፡ ከላይ ያሉትን ሁለቱን ዋና ባለስልጣናት ለማግኘት ቀርቶ ደብዳቤ ወደ ሚመለከተው መመራቱን እንኳን ከሁለት ሶስት ቀናት በሁዋላ በስልክ ነው የሚነገረው፡፡፡

ለዘመናት የገዘፈ ህንጻውን እያየሁ የማደንቀው እናት መ/ቤቴ ትምህርት ሚኒስቴር የደንበኛ አገልግሎትን በዚህ መሰል መንገድ ሲያስተናግድ ማየቴ እጅግ በጣም አሳፍሮኛል፡፡ ከደንበኛ አገልግሎት አሰጣጥ ባለፈ፤ ተማሪዎች በመከራና በጭንቅ ውስጥ ሆነው የተፈተኑትን የፈተና ውጤትን በተገቢው መንገድ አለማረምና ተገቢውን ውጤት አለመስጠት ግን የሚኒስቴር መ/ቤቱ ትልቁ የታሪኩ ጥቁር ነጥብ ሆኖ መመዝገቡ፡ እጅግ ያሳፍራል፡፡ ሁሉንም አይነስውራን ተማሪዎች ኖርማል ብሎ ጉዳታቸውን በይፋ መካድና  በማይገባቸው ነጥብ መገምገም፡ይህንንም ስህተት ለመቀበል ያለው አንባጓሮ እጅግ አሳፋሪ ነው፡፡ በበርካታ የሀገሪቱ ክፍሎች ጦርነቶች ቢኖሩም በተወሰኑ ቦታዎች ያለው አንጸራዊ ሰላም ለተወሰኑ ተማሪዎች አንጻራዊ የሆነ ጠቀሜታ ስላለው በተለያየ ሜዳ የተጫወቱ ተጫዋቾችን በተመሳሳይ ዳኛ መዳኘት ግን ተገቢ አይደለም፡፡  የዚህ አመት የትምህር ሚኒስቴር ስህተት ስህተቱን መስራቱ ብቻ ሳይሆን ስህተቱን ተቀብሎ አለማስተናገዱ፡ ስህቱን ለመቀበልም ዝግጁ የሆኑ ባለሙያዎችና አመራሮች አለመኖራቸው ነው፡፡



                             ገበር አምባ                    ስራ ፈቶ ሲያሽ ያንች ተመልካች                       በውበት ቁንጅና ማን ነበር እንዳንች፡፡          ...